Monday, January 5, 2009

ወ/ሪት ብርቱካን ዛሬም ሆነ ነገ ሊቀመንበራችን ናቸው

ከወላጅ እናታቸው ውጪ ማንም አልጎበኛቸውም

ከታሰሩ አንድ ሳምንት ያለፋቸውን የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ሊቀመንበር ወ/ሪት ብርቱካን ሚዴቅሳን ለመጠየቅ ወደቃሊቲ ያቀኑ ወዳጅ ዘመዶቻቸውና የትግል አጋሮቻቸው ለአውራምባ ታይምስ ዝግጅት ክፍል እንደገለጹት ሊቀመንበሯን ለመጠየቅ ወደ ቃሊቲ ካመሩ ወገኖች ውስጥ ከወላጅ እናታቸው ውጪ ገብቶ እንዲጠይቅ ለማንም አለመፈቀዱን አብራርተዋል፡፡በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጡ አውራምባ ታይምስ ጥያቄ ያቀረበላቸው የማረሚያ ቤቱ አስተዳዳሪ አቶ አበበ ዘሚካኤል ምንም አይነት ማብራሪያ ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡ አንድነት ፓርቲ በበኩሉ በትናንትናው ዕለት ባወጣው ባለ 12 ነጥብ የአቋም መግለጫ ‹ለእውነተኛ የህግ የበላይነት መከበር በጽናት ቆመው ለእስር የበቁ ሊቀመንበራችንን ለማስፈታት በመላው አለም ያሉ ኢትዮጵያዊያን የተቃውሞ ድምጻቸውን ያሰሙ› ሲል ጥሪ አቅርቧል፡፡