Wednesday, January 21, 2009

የአውራምባ ታይምስ አዘጋጅ በ3000 ብር ዋስ ተለቀቀ

በአውራምባ ታይምስ ጋዜጣ የሚያዝያ፣ግንቦትና ሰኔ ወር እትሞች ላይ በተስተናገዱ ሦስት ርዕሰ አንቀጾች፣ አንድ መጣጥፍና አንድ ቃለምልልስ ምክንያት ዓቃቤ ህግ ‹ህዝብን ለሁከት በማነሳሳት ወንጀል› ክስ የተመሰረተበት የአውራምባ ታይምስ ጋዜጣና መጽሄት ዋና አዘጋጅ ዳዊት ከበደ ዛሬ ረቡዕ ጉዳዩን የተመለከተው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አስረኛ ወንጀል ችሎት በብር 3000 ሺህ ዋስ ለየካቲት 13/2001 እንዲቀርብ ብይን ሰጠ፡፡
ለዋና አዘጋጁ መከሰስ ምክንያት ከሆኑት ዘገባዎች መካከል በጋዜጣው የግንቦት 26 ቀን 2000 ዓ.ም ዕትም የወጣውና ‹ስልጣኔን እለቃለሁ ሲባል ስለ ትውፊትም(legacy) ማሰብ ተገቢ ነው› የሚል ርዕሰ አንቀጽ ይገኝበታል፡፡ጠ/ሚ መለስ በሶስት አመት ውስጥ ስልጣናቸውን እንደሚለቁ በተናገሩ በጥቂት ቀናት ውስጥ የተጻፈው ይህ ርዕሰ አንቀጽ ጠ/ሚኒስትሩ ስልጣን ሲረከቡ የገቧቸውን ቃሎች አለማክበራቸውን ብዙ ማስረጃዎችን በማቅረብ ይተነትንናል፡፡ ጠ/ሚኒስትሩ ወደ ስልጣን ሲመጡ የኢትዮጵያ ህዝብ በቀን ሦስት ጊዜ እንደሚበላ የገቡትን ቃል አሁን ካለው በሚሊዮን የሚቆጠር ረሀብተኛ ወገን ጋር በማነጻጸር እንዲሁም በአገሪቱ ያለውን የፍትህ እና የመልካም አስተዳደር እጦት ያትታል፡፡ በመጨረሻም ርዕሰ አንቀጹ ይህም ሆኖ ጠ/ሚኒስትሩ በቀሯቸው ሦስት አመታት ለመልካም ትውፊት(legacy) ሲሉ መልካም ነገሮችን እንዲሰሩ ይጠይቃል፡፡
ሁለተኛው የአቃቤ ህግ ማስረጃ በግንቦት 12/2000 የተስተናገደውና ‹በንቅናቄው ዙሪያ የምንለውን ለማለት ወደድን› በሚል ርዕሰ የቀረበ ርዕሰ አንቀጽ ሲሆን ይዘቱም አንዳንድ ወገኖች በሰላማዊ ትግል ተስፋ እንዲቆርጡ ያደረጓቸው ምክንያቶች ገለልተኛ መሆን የሚገባቸው ዴሞክራቲክ ተቋማት ገለልተኛ ሆነው የቤት ስራቸውን ባለመስራታቸው እንደሆነ በመዘርዘር አሁንም እነኚህን የቤት ስራዎች መንግስት ካልሰራ በአሁኑ ሰዓት በሰላማዊ ትግል አምነው በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኙ ወገኖችም ተስፋ ቆርጠው ተመሳሳይ አቋም ሊይዙ ስለሚችሉ ዛሬውኑ በአገሪቱ ዴሞክራታይዜሽን ሂደት ውስጥ በስፋት ሊያሳትፍ የሚችል አሰራር እንዲዘረጋ ርዕሰ አንቀጹ ይማጸናል፡፡ በርዕሰ አንቀጹ ማሳረጊያም ላይ የሚከተለው ሀረግ ይገኝበታል ‹በመጀመሪያ ደረጃ ጋዜጣችን በህግ የበላይነት ታምናለች፡፡ በአገሪቱ ያሉ መጥፎም ይሁኑ ጥሩ ህጎችን(ህግ እስከሆኑ ድረስ) እናከብራለን ስለንቅናቄው አንስተን የምንነጋገረው ዜጎች በአገር ውስጥም በውጪም የሚደረጉ አገራዊ እንቅስቃሴዎችን የማወቅ መብት ስላላቸው ነው› ይላል፡፡ ለአዘጋጁ መከሰስ ምክንያት ነው ተብሎ በአቃቤ ህግ የቀረበው የዶ/ር መረራ ቃለምልልስ ሲሆን ‹እኔ የምመርጠው ቢራ እየጠጡ መታገልን ነው› የሚል ርዕስ ባለው ቃለምልልስ ከቀረቡ በርካታ ጥያቄዎች አንዱ ምን አይነት የትግል ስልት ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን ያሰፍናል የሚል ይገኝበታል፡፡ ዶክተሩም የሌሎች አገሮች ተሞክሮን በማንሳት በምርጫ መምጣትና በትጥቅ ትግል መምጣት ብቻውን ዴሞክራሲያዊ መሪም ሆነ አምባገነን መሪ ለመሆን ምክንያት እንደማይሆን ገልጸው በምርጫ መጥተው አምባገነን የሆኑ መሪዎች የመኖራቸውን ያህል የኒካራጓው ሳንዲኒስታን የመሳሰሉ በትጥቅ ትግል ስልጣን ከጨበጡ በኋላ በምርጫ ተሸንፈው ከስልጣን በመውረድ እንደገና በሌላ ዙር ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ስልጣን የያዙበት ሁኔታ እንዳለ በመግለጽ እርሳቸውም ሆኑ ፓርቲያቸው ግን በሰላማዊ ትግል እንደሚያምኑ የገለጹበት ቃለምልልስ ይገኝበታል፡፡
ዋና አዘጋጁ ከጋዜጣው ጋር በተያያዘ በሌላ ተመሳሳይ ክስ የፊታችን ሰኞ ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ ይታወቃል፡፡